(ክንፉ አሰፋ)
በተንጣለለ ቪላ ውስጥ ከበድ ያሉ እንግዶች “ጸዳ” ባሉ ምግብና መጠጦች እየተስተናገዱ ነው። ታዋቂ ግለሰቦች፤ ባለስልጣናት እና አርቲስቶች የቀረበላቸውን ብፌ በልማታዊ ወጋቸው እያወራረዱ ሳሉ አንድ እንግዳ ነገር በመሃላቸው ተከሰተ። ሞቅ ባለው የአይቴ ነጋ ገብረእግዚአብሄር ድግስ ላይ ያልተጋበዙ ሁለት ሰዎች ዘው ብለው ከግብዣው ክፍል ገቡ። የፌዴራል ፖሊስ አባላት ነበሩ።
በዚህ ያልተለመደ ክስተት የአቶ ነጋ እንግዶች አልተደናገጡም ነበር። ይልቁንም የፌዴራል ፖሊሶቹ ለተጨማሪ ጥበቃ የመጡ ነበር የመሰላቸው። አንድ ብርጌድ ያህል ጦር አስከትለው የመጡት ፖሊሶች ግን አቶ ነጋ ገብረእግዚአብሄርን አስጠሯቸው። አቶ ነጋም ለጥሪው እንደወትሮው በመወጣጠርና ፍጹም ትእቢት በተሞላበት አነጋገር ምላሽ ሰጡ። በፖሊስ አባላቱ እና በአቶ ነጋ መካከል የሃይለ-ቃል ልውውጥ ተጀመረ። እሰጥ እገባው አንድ፣ ሁለት እያለ ሄደና በመጨረሻ ተካረረ። በዚህ ሰዓት አቶ ነጋ ስልክ መደዋወል ያዙ። ከፍተኛ የሚባሉ ባለስልጣናትና ምኒስትሮች ጋ ደወሉ። ከዚያም በመቀጠል፣ ጀነራሎች ጋ ደወሉ… የጦር መኮንኖች፣ የፓርቲ ባለስልጣናት… ሁሉም ጋ ተደወለ። የባለስልጣናቱ ምላሽ ግን ጥሩ እንዳልነበር ከአቶ ነጋ ፊት ላይ ይነበብ ነበር። ወዳጆቻቸው ሁሉ እንደ ቱኒዚያው ቤን አሊ በአንድ ጊዜ ከዷቸው።
“በል – ና – ውጣ!” አለ አንደኛው የፖሊስ አባል፣ የስልኩን ሽርጉድ በጥሞና ከተከታተለ በኋላ።
“ምን ማለትህ ነው? እኔኮ ነጋ ነኝ። ነጋ ታሪኩ!” አሉ። አነጋገራቸው የጀምስ ቦንድን ይመስል ነበር። በዚህ ጊዜ ታዲያ እጃቸውም አላረፈም። ከጎን ያሸጎጡትን መሳርያ ለማውጣትም ዳዳቸው።
በቅጽበት ግን ፌዴራል ፖሊሱ ቀደማቸው። በድንገት “ጯ!” የሚል ድምጽ አዳራሹን አናጋው። የፖሊሱ አይበሉባ የግራ መንጋጭላቸው ላይ ሲያርፍባቸው ጊዜ፤ አይቴ ነጋ ነገር አለሙ ተደበላለቀባቸውና እጅ መስጠትን መረጡ። ግብር ሊያበሉ በጠሯቸው የክብር እንግዶቻቸው ፊት፣ ከዚህ በላይ መዋረድ አልፈቀዱም። ሁለት እጃቸውንም ወደ ፖሊሱ በመዘርጋት ለብረት ማሰርያው ራሳቸውን አመቻቹ። እጃቸው የኋሊት ከተጠፈረ በኋላም አቶ ነጋ እንዲህ አሉ። “በቃ! ህወሃት አበቃለት!”